ይህ የአፈጻጸም ክርክር የተጀመረዉ በአማራ ክልል በዳህና ወረዳ ፍ/ቤት ሲሆን የአሁን አመልካች የሥር ፍርድ ባለመብት፣ የአሁን ተጠሪ የሥር የፍርድ ባለዕዳ ሆኖ ሲከራከሩ ነበር፡፡ ጉዳዩ ለዚህ ሰበር ችሎት ሊቀርብ የቻለዉ አመልካች የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ.ቁ.0337693 ሰኔ 15 ቀን 2015 ዓ.ም የሰጠዉ ዉሳኔ መሰረታዊ የሆነ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ስለሆነ እንዲታረምልኝ በማለት በማመልከታቸዉ ነዉ፡፡
የጉዳዩ አመጣጥ ሲታይ በግራ ቀኛዉ መካከል በነበረዉ የይዞታ ክርክር የሥር የወረዳዉ ፍ/ቤት የአሁን ተጠሪ ለክርክር መነሻ የሆነዉን ይዞታ ለቆ ለአመልካች እንዲያስረክብ መወሰኑን መዝገቡ ያሳያል፡፡ የአሁን አመልካች ፍርዱን ለማስፈጸም የአፈጻጸም አቤቱታ ያቀረበ ሲሆን የወረዳዉ ፍ/ቤቱ የአሁን አመልካች በይዞታዉ ላይ ባለመብት ከመሆኑ በፊት የአሁን ተጠሪ በይዞታዉ ላይ ሁለት ክፍል ያለዉን ቤት መስራቱን በማረጋገጥ አመልካች የቤቱን ግምት ለተጠሪ እንዲከፍልና ተጠሪ ይዞታዉን ለቆ ለአመልካች እንዲያስረክብ ብይን መስጠቱን የዉሳኔዉ ግልባጭ ያመለክታል፡፡ በየደረጃዉ ያሉት የክልሉ ፍ/ቤቶችም የቀረበላቸዉን ቅሬታ ዉድቅ በማድረግ የሥር ፍ/ቤትን ዉሳኔ በማጽናት መወሰናቸዉን የሥር ፍ/ቤት የዉሳኔ ግልባጭ ያሳያል፡፡ የአሁን የሰበር አቤቱታ የቀረበዉ በዚህ ዉሳኔ ቅር በመሰኘት ለማስለወጥ ነዉ፡፡
የአሁን አመልካች መስከረም 4 ቀን 2016 ዓ.ም በተጻፈ የሰበር አቤቱታ፡ የአሁን ተጠሪ በዋናዉ ጉዳይ ላይ ተከራክሮ የቤት ግምት ካሳ እንዲከፈለዉ የፍርድ ባለመብት ባልሆነበት የሥር ፍ/ቤት በዋናዉ ፍርድ የቤት ግምት ካሳ ጉዳይ ለተጠሪ እንዲከፈል ባልተወሰነበት፣ ተጠሪ በይዞታዉ ላይ በሕገወጥ መንገድ ቤቱን ሲሰራ አመልካች እየተቃወምኩት መሆኑን ተረጋግጦ ባለበት የሥር ፍ/ቤት በዋናዉ ፍርድ መሰረት ለክርክር መነሻ የሆነዉን 10 በ15 ካ.ሜ የሆነዉን ይዞታ ተጠሪ ለአመልካች እንዲለቅ ማስፈጸም ሲገባዉ አመልካች ለተጠሪ የቤቱን ግምት እንዲከፍል መወሰኑ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ እንዲታረምልኝ በማለት በዝርዝር አመልክቷል፡፡መልካም ንባብ….