የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች በ2014 የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የፍትሐብሔር ጉዳዮች ፍሰት አስተዳደርን ተግባራዊ በማድረግ እና በመዛግብት አፈጻጸም ያስመዘገቡት ውጤት አበረታች በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባው የፍርድ ቤቱ ፕሬዚደንት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ገለጹ፡፡
ክብርት ፕሬዚደንትዋ ይህን የገለጹት የፍርድ ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች፣ ዳኞች እና ረዳት ዳኞች በተሳተፉበትና በፌደራል ፍ/ቤቶች የአምስት ዓመታት (2014-2018 ዓ.ም) ስትራቴጂያዊ ዕቅድ ዋና ዋና ይዘት እና በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የችሎቶችና ዳኞች የ2014 የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የመዛግብት አፈጻጸም ላይ መጋቢት 3 ቀን 2014 ዓ.ም በካፒታል ሆቴል የተደረገውን ውይይት ሲያጠቃልሉ ባደረጉት ንግግር ነው፡፡