ክቡራንና ክቡራት ዳኞች
ያጠናቀቅነው የ2013 ዓ.ም በፍርድ ቤታችን ጉልህ የሚባሉ የማሻሻያ ሥራዎች የተከናወኑበትና በዚህ ረገድ በቀጣይ ለሚመዘገቡ ስኬቶች መሠረት የተጣለበት ሆኖ የሚወሰድ ነው፡፡
ባሳለፍነው ዓመት ለፍርድ ቤቱ የማሻሻያ ሥራ መሠረታዊ ከሆኑት እና በፍርድ ቤቶች የዳኞችን እና ተቋማዊ ነጻነትን፣ ገለልተኝነትን እንዲሁም ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ ከተወሰዱ እርምጃዎች መካከል የተሻሻሉት የፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ እና የፌደራል የዳኝነት አስተዳደር አዋጅ በሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ፀድቀው ወደሥራ መግባታቸው ጉልህ ሥፍራ የሚሰጠው ነው፡፡
እነዚህን አዋጆች ተግባራዊ ለማድረግም በርካታ ደንቦችና መመሪያዎች እየተዘጋጁና እየጸደቁ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ ከእነዚህ መካከል የጉዳዮች ፍሰት አስተዳደር መመሪያ እና የዳኞች ሥነምግባር እና የዲሲፒሊን ሥነሥርዓት ደንብ የፀደቁ ሲሆኑ በቅርቡ ፀድቀው ወደትግበራ እንደሚገቡ ከሚጠበቁት መካከል የአስተዳደር ሰራተኞች መተዳደሪያ ደንብ እና የዳኞች የሥራ አፈጻጸም ምዘና መመሪያ ይጠቀሳሉ፡፡