የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በሕገ መንግስቱ እና በሕግ በተሰጣቸው ስልጣንና ኃላፊነት መሰረት የሚቀርቡ ጉዳዮችን በማስተናገድ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን፣ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች እንዲጠበቁ ሰላም እና ስርዓት እንዲከበር የማድረግ ተግባራትን እየተወጡ ይገኛሉ፡፡
በዚህ መሰረት በ2015 በጀት ዓመት በነበረዉ የመዛግብት አፈጻጻም አንጻር ለፌዴራል ፍርድ ቤቶች በአጠቃላይ 213,116 መዛግብት ቀርበዋል። ከእነዚህም ዉስጥ ለ184,467 (86.56%) መዛግብት እልባት መስጠት የተቻለ ሲሆን 28,675 (13.44%) መዛግብት ደግሞ ወደ 2016 በጀት ዓመት ተሻግረዋል፡፡ የበጀት ዓመቱ አፈጻጸም ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ2014 በጀት ዓመት ለፌ/ፍ/ቤቶች የቀረቡት 209,317 መዛግብት ሲሆኑ ዕልባት ያገኙት ደግሞ 176,767 ነበሩ፡፡ በዚህም መሠረት በ2015 በጀት ዓመት የቀረቡት መዛግብት በ2014 በጀት ዓመት ከቀረቡት በ3,799 (1.8%) ከፍ ያሉ ሲሆን በተመሳሳይ ዕልባት ያገኙትም በ7,670 (4.3%) መዛግብት ከፍ ያሉ ናቸው፡፡
የፍርድ ቤቶቹ አፈጻጸም በተናጠል ሲታይ ለፌ/ጠ/ፍ/ቤት በ2015 በጀት ዓመት 26,185 መዛግብት ቀርበው ለ19,201 ዕልባት የተሰጠ ሲሆን 6,984 መዛግብት ወደ 2016 በጀት ዓመት ተሻግረዋል፡፡ በተመሳሳይ በ2015 በጀት ዓመት ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የቀረቡት የመዛግብት ብዛት 33,721 ሲሆን 26,301 መዛግብት ዕልባት አግኝተዋል፡፡ ወደ 2016 የተሻገሩት መዛግብት ብዛትም 7,420 ሆኗል፡፡ እንዲሁም ለፌ/መ/ደ/ፍ/ቤት በ2015 በጀት ዓመት የቀረቡት 153,210 መዛግብት ሲሆኑ 138,965 ዕልባት በማግኘታቸው 14,245 ወደ 2016 በጀት ዓመት ተላልፈዋል፡፡