Friday, June 13, 2025 / Categories: News የኢ-ፋይሊንግ እና የፕላዝማ ችሎት የስራ ማስጀመሪያ መርሃግብር ተካሄደ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ጋር በመተባበር በገላን ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ቤት ማዕከል ያሰራውን የኢ-ፋይሊንግ እና የፕላዝማ ችሎት ሰኔ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በይፋ ስራ አስጀምሯል፡፡ በመርሃግብሩ ንግግር ያደረጉት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ክቡር አቶ ቴዎድሮስ ምህረት የፕላዝማ ችሎት ከዚህ ቀደም በስራ ላይ የነበረ ቢሆንም አሁን የተሰራው የፕላዝማ ችሎት በጥራትም ሆነ በተመሳሳይ ሰዓት ታራሚዎችን በበርካታ ችሎቶች ማስተናገድ የሚያስችል መሆኑና በኢ-ፋይሊንግ ስርዓቱ አማካኝነት በፍርድ ቤቱና በማረሚያ ቤቱ መካከል በኤሌክትሮኒክስ ዘዴ ሰነዶችን እና መረጃ መለዋወጥ ማድረግ የሚያስችል መሆኑ የተለየ ያደርገዋል ብለዋል፡፡ አክለውም ታራሚዎች በፍርድ ቤት በሚኖራቸዉ ምልልስ ምክንያት የሚፈጠረዉን ጫና በማስቀረት ደህንነታቸዉ ተጠብቆ ባሉበት ማረሚያ ቤት ሆነዉ ያለ ምንም እንግልት የችሎት አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል ቴክኖሎጂ መሆኑን ገልፀው ቴክኖሎጂውን ያለሙ የፍርድ ቤቱን የአይሲቲ ባለሙያዎች እና በቴክኖሎጂው መተግበር ፍቃደኛ ከመሆን አልፈው ቀና ትብብር ያደረጉትን የማረሚያ ቤቱን ኃላፊዎች አመስግነዋል፡፡ የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል የኑስ ሙሉ በበኩላቸው ማረሚያ ቤቱ ይህንን የቴክኖሎጂ ዉጤት መጠቀሙ ታራሚዎች የተፋጠነ ፍትህ እንዲያገኙ፣ መረጃዎች ከሰዉ ንክኪ በፀዳ መንገድ ለሚመለከተዉ አካል እንዲደርሱ፣ የመልካም አስተዳደርና ብልሹ አሰራሮች ጋር ተያይዞ የሚነሱ ችግሮች ለመፍታት፤ የመረጃ አያያዝ ስርዓትን ለማዘመን፤ ግልፅነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት አሰራር ለመዘርጋት የሚረዳ እንዲሁም የማረሚያ ቤቱን የስራ ጫና እና የሰዉ ሃይል እጥረት በከፍተኛ ደረጃ የሚያቃልል መሆኑን በመግለፅ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱን አመስግነዋል:: በመርሀ ግብሩ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢፌዴሪ ፍትህ ሚንስቴር ሚኒስትር ድኤታ፣ የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀኔራል እና ም/ኮሚሽነሮች ጀኔራሎች ፣የኢፌዴሪ ህግና ፍትህ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር፤ የኢፌዴሪ ፍትህ ሚኒስቴር ተጠሪ ተቋማት የስራ ኃላፊዎች እና የሌሎች ተቋማት ተወካዮች ታድመዋል፡፡ Previous Article ፍርድ ቤቱ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ Next Article በወንጀል ነክ ድርጊት ዉስጥ ገብተዉ ከተገኙ ህጻናት እንዲሁም በሴቶች እና ህጻናት ችሎት ለሚሰሩ የፌዴራል ዳኞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ Print 548