የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሀዋሳ ማዕከል በይፋ አገልግሎት መስጠት ጀመረ
የፌዴራል ጉዳዮችን በውክልና እንዳይመለከቱ ስልጣናቸው በተነሳባቸው የክልል ፍርድ ቤቶች የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተዘዋዋሪ ችሎት በማደራጀት አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡
በደቡብ ክልል የፌዴራል ጉዳዮችን በተዘዋዋሪ ችሎት አገልግሎት እየሰጠ የቆየው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ለዳኝነት የሚቀርቡ ጉዳዮች እየጨመሩ በመምጣታቸውና የሚሰጠውን የዳኝነት አገልግሎት ቅልጥፍና ለማሳደግ ይረዳ ዘንድ በሐዋሳ ከተማ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቅርንጫፍ ማዕከል ማቋቋም አስፈላጊነት በአመራሩ ታምኖበት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆይቷል፡፡
አዲስ የተደራጀው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሃዋሳ ማዕከል ከሚያዚያ 15-18 ቀን 2013 ዓ.ም በሃዋሳ በተካሄደ የፌዴራልና የክልል ፍርድ ቤቶች እና የፍትህ አካላት ከፍተኛ አመራሮች አመራሮች በተገኙበት በተካሄደ የጋራ የምክክር መድረክ በይፋ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል፡፡
የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሃዋሳ ማዕከል ስራ መጀመር የፌዴራል ጉዳዮችን ተቀብሎ ዳኝነት የሚሰጥ አደረጃጀት ከመፍጠሩም በላይ ዳኞች፤ ሬጂስትሮች፤ ተከላካይ ጠበቆችና ሌሎች ባለሙያዎች በማዕከሉ በቋሚነት ተመድበው አገልግሎቱ በቀጣይነት እንዲሰጥ ያግዛል መባሉን ከፍርድ ቤተ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ የሚሰጠው የዳኝነት አገልግሎት ተደራሽነት እና ቅልጥፍና ይሻሻል፡፡ የዳኞች እና የተከላካይ ጠበቆች እንዲሁም የባለጉዳዮች እንግልት በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል ተብሏል፡፡
መረጃው ከፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ኮሚዩኒኬሽ ክፍል የተገኘ ነው፡፡
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት
400